1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የምርጫ ቦርድ እና የሲፌፓ እሰጥ አገባ

ሰኞ፣ ሚያዝያ 28 2016

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሲዳማ ፌዴራሊስት ፓርቲ ሊሰረዝ እንደሚችል አስጠንቋቋል። አንዳንድ የፓርቲው አመራሮች በቦርዱ ላይ የሥም ማጥፋት መረጃዎችን ከማሰራጨት እንዲታቀቡ አሳስቧል፡፡ የቦርዱን ወቀሳ ያጣጣለው የሲዳማ ፌዴራሊስት ፓርቲ “ቦርዱ በፓርቲው ላይ ተገቢ ያልሆነ ወሳኔ በማሳለፍ ፓርቲውን አደጋ ላይ እየጣለ ይገኛል“ ብሏል፡፡

https://p.dw.com/p/4fYZo
የሲዳማ ፌድራሊስት ፓርቲ ጽህፈት ቤት በሐዋሳ
የሲዳማ ፌዴራሊስት ፓርቲ የቀድሞው ሊቀመንበር ረዳት ፕሮፌሰር ተሰማ ኤሊያስ ከሀገር መውጣታቸውን ተከትሎ ከተተኪ አመራሮች ህጋዊነት ጋር ተያይዞ የተነሳው ጥያቄ በፓርቲው ውስጥ  ለተፈጠረው አለመግባባት ምክንያት መሆኑ ነው የሚነገረው ፡፡ምስል Shewangizaw Wegayoh/DW

የምርጫ ቦርድ እና የሲፌፓ እሰጥ አገባ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሲዳማ ፌዴራሊስት ፓርቲ ሲፌፓን አስመልከቶ ያወጣው መግለጫ በዋናነት ከኦዲት ሪፖርት አለመቅረብና በሥም ማጥፋት ቅሬታ ላይ ያተኮረ ነው ፡፡ ቦርዱ በዚሁ መግለጫው  “ የሲዳማ  ፌዴራሊስት ፓርቲ ሲፌፓ የመሰረዝ ዕጣ ፋንታ ሊገጥመው ይችላል “ ብሏል  ፡፡ ፓርቲው ሊሠረዝ ይችላል ያለው በድጋፍ መልክ ለወሰደው1 ነጥብ 1 ሚሊየን ብር እስከአሁን የሂሳብ ሪፖርት ባለማቅረቡ መሆኑንም አስታውቋለ፡፡ አንዳንድ የፓርቲው አመራሮች በቦርዱ ላይ የሥም ማጥፋት መረጃዎችን ከማሰራጨት እንዲታቀቡ ሲልም ቦርዱ አስጠንቅቋል፡፡

የአመራሮቹ አለመግባባትና  የቦርዱ መግለጫ   

የሲዳማ ፌዴራሊስት ፓርቲ የቀድሞው ሊቀመንበር ረዳት ፕሮፌሰር ተሰማ ኤሊያስ ከሀገር መውጣታቸውን ተከትሎ ከተተኪ አመራሮች ህጋዊነት ጋር ተያይዞ የተነሳው ጥያቄ በፓርቲው ውስጥ  ለተፈጠረው አለመግባባት ምክንያት መሆኑ ነው የሚነገረው ፡፡ አስቀድሞም የፓርቲው ተቀዳሚ ምክትል ሊቀመንበር መሆናቸውን የጠቀሱት አቶ ጴጥሮስ ዱቢሶ  የምርጫ  ቦርድ በፓርቲው ህገ ደንብ መሠረት  ከአገር የወጡትን ሊቀመንበር ቦታ ተክተው እንዲሠሩ እንደወሰነላቸው ይናገራሉ ፡፡ በአንጻሩ የፓርቲው ጽህፈት ቤት ሃላፊ መሆናቸውን የሚናገሩት አቶ ገነነ ሀሰና ደግሞ አቶ ጴጥሮስን ጨምሮ ሌሎች አመራሮች ቀደም ሲል በሥነሥረዓት ጥሰት ከሃላፊነት የታገዱ መሆናቸውን በመጥቀስ የምርጫ ቦርድ ውሳኔ አግባብ አይደለም ይላሉ ፡፡

የሲፌፓ አቤቱታ እና የምክር ቤቱ ምላሽ

በዚህ ውዝግብ መኻል መግለጫ ያወጣው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ፓርቲው የመሠረዝ ዕጣ ፋንታ ሊገጥመው እንደሚችል አስታውቋል ፡፡ ቦርዱ “ ፓርቲው ሊሠረዝ ይችላል “ ያለው በ2015 ዓም በድጋፍ መልክ ለወሰደው 1 ነጥብ 1 ሚሊዬን ብር እስከአሁን የሂሳብ ሪፖርት ባለማቅረቡ መሆኑን  ጠቅሷል፡፡ ቦርዱ በተጨማሪም “ አንዳንድ “ ሲል የጠራቸው የፓርቲው አመራሮች በቦርዱ ላይ የሥም ማጥፋት መረጃዎችን ከማሰራጨት እንዲታቀቡ ሲልም አስጠንቅቋል፡፡

መግለጫው በአመራሮቹ ዕይታ

ዶቼ ቬለ በሲፌፓ ዙሪያ በወጣው መግለጫ ላይ ተጨማሪ ማብራሪያ ለመጠየቅ የብሄራዊ ምርጫ ቦርዱ የሥራ ሃላፊዎችን ለማነጋገር ያደረገው ጥረት አልተሳካለትም ፡፡ ከኦዲት ሪፖርት አለመቅርብና ከሥም ማጥፋት ጉዳይ ጋር ተያይዞ ቦርዱ ባወጣው መግለጫ ዙሪያ አስተያየታቸውን የተጠየቁት የፓርቲው ጽህፈት ቤት ሃላፊው አቶ ገነነ ሀሰና የቦርዱን ወቀሳ አልተቀበሉትም ፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሎጎ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ «የሲዳማ ፌዴራሊስት ፓርቲ ሲፌፓ የመሰረዝ ዕጣ ፋንታ ሊገጥመው ይችላል» ብሏልምስል National Election Board of Ethiopia

ይልቁንም ቦርዱ በፓርቲው ላይ ተገቢ ያልሆነ ውሳኔ በማሳለፍ ፓርቲውን አደጋ ላይ እየጣለ ይገኛል በማለት የተናገሩት አቶ ገነነ  “ በድጋፍ የወሰድነውን ሂሳብ በማወራረድ ሪፖርት ማቅረብ እንዳለብን እናውቃለን ፡፡ የሂሳብ ሪፖርቱን መሥራት ያልቻልነው ግን ቢሮው በአንድ ግለሰብ ቁጥጥር ሥር በመሆኑ የአስፈጻሚውም ሆነ የቁጥጥር ኮሚሽን አባላት ወደ ቢሮ ገብተው ሊሠሩ አልቻሉም ፡፡ ምርጫ ቦርድ ይህን ጉዳይ እልባት እንዲሰጠን ብንጠይቅም ሊሰማን አልቻለም ፡፡ ቦርዱ ሥም ማጥፋት በሚል የቀረበውም ትክክል አይደለም ፡፡ በህጋዊ የማህበራዊ ድህረ ገጻችን ላይ የጉዳዩን  ሂደት ከማሳወቅ ውጭ ሌላ ያቀረብነው ነገር የለም “ ብለዋል ፡፡

የቀረበው ጥሪ

ፓርቲውን ከአገር የወጡትን ሊቀመንበር ተክተው እንዲሠሩ የምርጫ ቦርድ እንደወሰናለቸው የሚናገሩት  አቶ ጴጥሮስ ዱቢሶ ግን የአቶ ገነነ ሀሰናን ሀሳብ አይቀበሉትም ፡፡ እንዳውም አሁን ለተፈጠረው ሁኔታ ተጠያቂው እነሱ ናቸው ይላሉ አቶ ጴጥሮስ  ፡፡ እነኝህ [ አመራሮች ] ወደ ቢሮ እንዲመጡ ህዳር 12 2016 ዓ.ም ደብዳቤ ጽፈናል ፣ በስልክም ጥሪ አድርገናል ፣ ምርጫ ቦርድም ጥረት አድርጓል ፡፡ ነገር ግን ውይይት ለማድረግም ሆነ ለመምጣት አልፈለጉም ፡፡ ይልቁንም እኛንም ሆነ የምርጫ ቦርዱን መክሰስን መርጠዋል ፡፡ አሁንም የሂሳብ ኦዲት ባለማስደረግ ፓርቲውን እያፈረሱ ያሉት እነሱ ናቸው ፡፡ ነገ እውነቱ እየጠራ ይመጣል ፡፡ በህዘብ የሚጠየቁ እነሱ ይሆናሉ  “ ብለዋል ፡፡

አዲሱ የሲዳማ ፌዴራሊስት ፓርቲ «ሲፌፓ»

አሁን ላይ ህጋዊ የፓርቲው አመራር እሳቸው መሆናቸውን የጠቀሱት አቶ ጴጥሮስ “ ከፓርቲው ጽህፈት ቤት ይዘው የወጡት ማህተምና  አርማ አግባብ ባለሆነ መንገድ እየተጠቀሙበት ይገኛሉ ፡፡ የተለያዩ ተቋማትም ሆነ የሚዲያ አካላት መገናኘት ያለባቸው ህጋዊ ዕውቅና ከተሠጠው አካል ጋር ብቻ ሊሆን ይገባል “ ብለዋል ፡፡
በሲዳማ ክልል አማራጭ ተፎካካሪ ፓርቲ ለመሆን በ2014 ዓ.ም የተመሠረተው የሲዳማ ፌዴራሊስት ፓርቲ በአሁኑ ወቅት ከ30 ሺህ በላይ አባላት እንዳሉት ከፓርቲው ድህረ ገጽ የተገኘው መረጃ ያመለክታል ፡፡

ሸዋንግዛው ወጋየሁ
እሸቴ በቀለ
ዮሐንስ ገብረእግዚዓብሔር